Home Uncategorized Newes በአገር አቀፍ ደረጃ ያሉ አምቡላንሶች አላግባብ መጠቀምን ለመግታት እና አምቡላንሶች ለታለመላቸው ዓላማ...

በአገር አቀፍ ደረጃ ያሉ አምቡላንሶች አላግባብ መጠቀምን ለመግታት እና አምቡላንሶች ለታለመላቸው ዓላማ ብቻ እንዲውሉ ሊወሰዱ ስለሚገባቸው እርምጃዎች የመጀመሪያ ደረጃ ሀገራዊ የምክክር መድረክ ተካሄደ።

0

የጤና ሚኒስቴር የጤና አገልግሎትን ከማስፋት እና ተደራሽ ከማድረግ አንፃር አገልግሎት አሰጣጡን በተሻለ ና በተደራጀ መልኩ ለማሳለጥ በ2015 ዓ.ም በጀት ዓመት ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ራሱን በአዲስ መልክ በማዋቀር ካደራጃቸው የስራ ክፍሎች መካከል አንዱ በጤና አገልግሎትና ፕሮግራም ዘርፍ ስር የሜዲካል አገልግሎት መሪ ስራ አስፈፃሚ መሆኑን የተናገሩት ዶክተር ኢሉባቡር ቡኖ በጤና ሚኒስቴር የሜዲካል አገልግሎት መሪ ስራ አስፈፃሚ ናቸው፡፡

ዶክተር ኢሉባቡር አክለውም ህሙማን ወደ ጤና ተቋም ደርሰው ተገቢውን ህክምና አገልግሎት እስኪያገኙ ድረስ አፋጣኝ የመጀመሪያ ህይወት አድን ህክምና የሚያገኙት በአምቡላንስ አገልግሎት እንደሆነ ገልፀው፤ የእናቶችና ህፃናትን ሞት ለመታደግ፣ ሰዎች ድንገተኛ አደጋ ሲገጥማቸው ተገቢውን የህክምና አገልግሎት ለመስጠት እንዲያችል አምቡላንሶች ለታለመላቸው ዓላማ ብቻ እንዲውሉ ብልሹ አሰራሮችን ተከታትሎ ማረም እንደሚገባም አፅንዖት ሰጥተው ተናግረዋል።

በጤና ሚኒስቴር የሜዲካል አገልግሎት መሪ ስራ አስፈጻሚ የቅድመ ጤና ተቋምና ቅብብሎሽ ዴስክ ኃላፊ የሆኑት አቶ ሲራክ ጉግሣ በዚህ ሀገር አቀፍ የምክክር መድረክ ላይ በአገር አቀፍ ደረጃ ያለውን የአምቡላን አጠቃቀም ተግዳሮቶች የሚያሳይ ገለፃ አቅርበው፤ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ በአምቡላንስ አጠቃቀም ላይ ያለውን ክፍተት አንገብጋቢ ችግር መሆኑን ተቀብሎ ከባለድርሻ አካላት ጋር በቀጣይ መወሰድ ስለሚገባቸው እርምጃዎች ለመወያትና ወደ ዘላቂ መፍትሄ ለመምጣት መዘጋጀቱን ገልፀዋል፡፡

አቶ ሲራክ እንደተናገሩት አምቡላንሶችን ከታለመላቸው ዓላማ ውጪ በሚጠቀሙ ክልሎች ላይ የሚከተሉት ችግሮች እንደተከሰቱ በተደረገ ክትትል መረጋገጡን ጠቅሰዋል፡፡ የአምቡላንስ ብልሽት መኖር፣ የአምቡላንስ ብክነት መኖር፣ የሀብት ብክነት፣ የህክምና አገልግሎት ጥራት መቀነስ፣ ማህበረሰብ ላልተፈለገ ወጪ መጋለጥ፣ ውስብስብ ለሆነ የህክምና አገልግሎት መጋለጥ ዋነኞቹ መሆናቸውንና ሁሉም በያገባኛል ስሜት ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባም ጠይቀዋል፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል የድንገተኛና ፅኑ ህሙማን ክፍል ፕሮፌሰር አክሊሉ አዛዥ አምቡላንስ አጠቃቀም ላይ ያደጉት አገራት ምን ዓየነት ተሞክሮ አላቸው የሚለውን አለማቀፋዊ ዳራ ከአገራችን ተጨባጭ ሁኔታ ጋር በማመሳከር ለተሻለ የአምቡላንስ አጠቃቀም የተሻለ ነው ያሉትን ገምቢ ሀሳቦች አክለው ገለፃ አቅርበው፣ በገጠሪቷ ኢትዮጵያ ያሉ ነፍሰ ጡር እናቶች አምቡላስ በትክክል በመጠቀማቸው በግማሽ ያህል እናቶችን ከሞት መታደግ መቻሉን በአንድ ወቅት የአለም አቀፍ ጆርናል እንደዘገበውም በማስረጃ አስደግፈው አቅርበዋል፡፡

በጤና ሚኒስቴር የህግ አገልግሎት መሪ ስራ አስፈፃሚ ባለሙያ የሆኑት ወ/ሪት ራህመት ሚፍታህ በበኩላቸው የአምቡላንስ አገልግሎትን በተመለከት ህጉ ምን ይላል እንዴት ይመራ የሚለውን የሚያመላክቱ የህግ ማዕቀፎችና ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አዋጁን ተከትሎ ያወጣውን መመሪያ አቅርበው በቀጣይ እስከታችኛው እርከን ድረስ ግንዛቤ የማስጨበጡ ስራ እንደሚቀጥልም ጠቁመዋል፡፡

ከግሉ ዘርፍ የጠብታ አምቡላንስ ተወካይ የሆኑት አቶ ይታገስ መንግስቱ ጠብታ አምቡላንስ ላለፉት አስራ አምስት ዓመታት ለህብረተሰቡ በመላው አገሪቷ አገልግሎት እየሰጠ እንደሀገር ያለውን አበርክቶ የሚያመላክት ገለፃ አቅረትበው ተሳታፊዎች ተወያይተውበታል፡፡

በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና ማህበራዊ ልማት፣ባህልና ስፖርት ቋሚ ኮሚቴ ተወካይ ዶ/ር ማህተሟ ሃይሌ የጤና ሚኒስቴር ዓመታዊ ሪፖርቱን ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሚያቀርብበት ሰዓት የአምቡላንስ አጠቃቀም ላይ ያሉ ተግዳሮቶች ተካተው አለማየታቸውን አንስተው፣በቀጣይ ተጠያቂነትን ለመዘርጋት የሚያስችል የህግ ማዕቀፍ እንዲኖር የበኩላቸውን አስተዋፅኦ እንደሚያደርጉ ቃል ገብተዋል፡፡

በዚህ ወሳኝ የምክክር መድረክ ላይ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና ማህበራዊ ልማት፣ባህልና ስፖርት ቋሚ ኮሚቴ ተወካዮች፣ የጤና ሚኒስቴር የማኔጅመንት አባላት፣ የተጠሪ ተቋማት ኃላፊዎች፣ የሆስፒታል ኃላፊዎች፣የክልል ጤና ቢሮ ኃላፊዎች፣ የቀይመስቀል ኢትዮጵያ ዋና ስራ አስኪያጅን ጨምሮ አጋር ድርጅቶች ተገኝተው በቀጣይ ምን ቢደረግ የተሻለ አገልግሎት መስጠት እንደሚያስችል የትኩረት አቅጣጫዎች ተቀምጧል፡፡

NO COMMENTS

LEAVE A REPLY

Please enter your comment!
Please enter your name here

Exit mobile version